EthiopiaSportSports

አዲሱ የፌዴሬሽን ህንፃ ህጋዊ የግዥ ስርዓትን ጠብቆ የተገዛ ነው አለ፡- የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፡፡

አዲሱ የፌዴሬሽን ህንፃ ህጋዊ የግዥ ስርዓትን ጠብቆ የተገዛ ነው አለ፡- የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን፡፡

ፌዴሬሽኑ ይሄን ያለው በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጠው መግለጫ ነው፡፡

በመግለጫው በወንዶች ፕሪምየር ሊግ የመጀመሪያ ዙር የትግራይ እና አማራ ክልል ክለቦች መካከል ለተፈጠረው ዕርቅ እጃቸው ላለበት አካላት ምስጋና በማቅረብ የጀመሩት የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ኢሳያስ ጂራ በቀጣይም ወደ ልማት ስራዎች እናተኩራለን ብለዋል፡፡

ፌዴሬሽኑ በአዲስ የህንፃ ግዥ ዙሪያ፣ ከአምብሮ ጋር ስላለው የትጥቅ ስምምነት እና የኢትዮጵያ ወንዶች ብሔራዊ ቡድን ነባራዊ ሁኔታ ላይ መግለጫ ትኩረት አድርጓል፡፡

ፌዴሬሽኑ አዲስ በገዛው ባለ ስምንት ወለል ህንፃ ግዥ ዙሪያ በሰጠው መግለጫ፤ የግዡ ሂደት ከአራት ዓመታት በፊት እንደጀመረ፣ በአፈፃፀም ችግር ምክንያት የግዡ ሂደት እንደተንጓተተ፣ በመቀጠል አዲሱ አመራር ከመጣ በኋላ በፌዴሬሽኑ ም/ፕሬዚዳንት ኮሎኔል አወል አብዱረህማን የሚመራ የ7 አባላት ኮሚቴ ተቋቁሞ ህጋዊ በሆነ መንገድ ከአንድም ሁለቴ ጨረታ በማውጣት የግዡ ሂደት እንደተጓዘ አቶ ኢሳያሰስ ተናግረዋል፡፡

ኮሎኔል አወል ደግሞ በግዡ ሂደት ከተለያዩ አካላት የተወጣጡ አማካሪዎችና ገምጋሚዎች እንደተሳተፉበት አስታውቀው፤ ኮሚቴው ባስቀመጠው መስፈርት መሰረት የቀረቡለትን ተመልክቶ ተገቢውን ህንፃ እንደመረጠ ተናግረዋል፡፡

የህንፃው ግዥ ከቫት በፊት በ86 ሚሊየን ብር የቀረበ መሆኑንና ኮሚቴው ከባለቤቱ ጋር ተነጋግሮ አንዲቀንስ በማድረግ በ83 ሚሊየን እንደተገዛ ገልፀዋል፡፡

አዲሱ የተገዛው ህንፃ ከፊፋ በመጣ ሶስት ሚሊየን ዶላር ሲሆን ወሎ ሰፈር አካባቢ እንደሚገኝ ተነግሯል፡፡

ከፊፋም ጋር በመነጋገር የግዡ ሂደት በጥቂት ወራት ውስጥ እንደሚጠናቀቅ እና ፌዴሬሽኑ እንደሚረከብ ፕሬዚዳንቱ ተናግረው፤ ለቤሮ አገልግሎት ከሚውሉት የህንፃ ክፍል ውጭ ያሉትን ለሌሎች አገልግሎቶች በማዋል የሚገኘው ገቢ ለእግር ኳስ የልማት ስራዎች እንደሚውል ተነግሯል፡፡

ከአምብሮ ጋር ስለተደረገው የትጥቅ ስምምነት በተያያዘ በተሰጠ መግለጫ ደግሞ ፌዴሬሽኑ ባለፉት ሁለት ዓመታት ለብሄራዊ ቡድን ትጥቅ ሲያቀርብ ከነበረው የጣሊያኑ ኢሪያ  ጋር ተለያይቶ ከእንግሊዙ አምብሮ ጋር ለዓራት ዓመታት እንደተስማማ ፕሬዚዳንቱ አቶ ኢሳያስ ተናግረዋል፡፡

ፌዴሬሽኑ ከኢሪያ ጋር ያለውን ውል ያቋረጠበት ዋንኛ ምክንያት የትጥቅ ጥራት ችግር ስላለበት መሆኑን አቶ ኢሳያስ ገልፀዋል፡፡

በዚህም የውሉ መቋረጥ ሂደት በህግ ጉዳይ የተያዘ ቢሆንም ፌዴሬሽኑ መቶ ሺ ዩሮ እንደሚከፍል ተነግሯል፡፡

ከአምብሮ ጋር ስምምነት ከመወሰኑ በፊት የተለያዩ አቅራቢዎችን ከተመለክትን በኋላ የአምብሮ አዋጭ በመሆኑ እንደተስማሙ ፌዴሬሽኑ አስታውቋል፡፡

አምብሮ ለደጋፊዎች በሚያቀርበው ምርትም ላይ ፌዴሬሽኑ የጥቅም ተጋሪ መሆኑ ተነግሯል፡፡

በመግለጫው ሌላው ትኩረት ደግሞ የኢትዮጵያ ወንዶች ብሄራዊ ቡድን ስለ ሚገኝበት ወቅታዊ ሁኔታ ሲሆን አሰልጣኝ አብርሃም መብርሃቱ ገለፃ አድርገዋል፡፡

ኢንስትራክተር አብርሃም ዋናው ብሄራዊ ቡድን በቅርብ ጨዋታ የሌለበት ቢሆንም ከፌዴሬሽኑ ጋር በተገኘ ይሁንታ፤ የፊፋን የወዳጅነት ካሌንደር ጠብቆ ያደርጋል ብለዋል፤ አሰልጣኙ ወጣቶቹ በኦሌምፒክ ማጣሪያ እና በሌሎች ውድድሮች ላይ በሚኖራቸው ዝግጅት ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በውጭ የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ተጫዋቾች ለብሄራዊ ቡድኑ እንዲያገለግሉ ለማድረግ ንግግር ስለመጀመሩ፤ እንዲሁም በአጠቃላይ በተለያዩ መስኮች በተለያዩ የእድሜ ደረጃ የሚገኙ ብሄራዊ ቡድን ለማሳደግ እየተሰራ እንደሆነ ኢንስትራክተር አብርሃም መብርሃቱ ተናግረዋል፡፡

Related Articles

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Back to top button