EthiopiaPoliticsSocial

በሰኔ 16ቱ የመስቀል አደባባዩ ላይ የተወረወረ አይነት ተመሳሳይ ቦምብ በተጠርጣሪ መኖሪያ ቤት ውስጥ ማግኘቱን መርማሪ ፖሊስ አስታወቀ።

 

መርማሪ ፖሊስ ዛሬ በተረኛ የጊዜ ቀጠሮን በሚመለከተው የፌደራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት 1ኛ ተረኛ ወንጀል ችሎት በቀረቡ ስድስት ተጠርጣሪዎች ላይ የደረሰበትን የምርመራ ደረጃ ለፍርድ ቤት ባስረዳበት ወቅት ተመሳሳይ ቦምብ ማግኘቱን አስታውቋል።

ከዚህ በተጨማሪም መርማሪ ፖሊስ ከሰኔ 16ቱ የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ ድጋፍ ሰልፍ ላይ የከቦምብ ፍንዳታ ጋር በተያያዘ ተጠርጥራ በአማኒኤል ሆስፒታል ከአይምሮ ህመም በህክምና ላይ የምትገኘውን የህይወት ገዳን ምርመራን ማቋረጡንም በዛሬው ችሎት አብራርቷል።

በችሎቱ በቀዳሚነት የተጠርጣሪ በየነ ቡላና የአብዲሳ መገርሳን የተደረሰውን የምርመራ ደረጃ አዳምጧል።

መርማሪ ፖሊስም በርካታ የምርመራ ስራዎችን ማከናወኑን በመጠቆም ተጨማሪ የኤፍ ቢ አይ የቴክኒክ ምርመራ ውጤትን እና መሰል ማስረጃዎቸን ለመቀበል ተጨማሪ የ14 ቀን ጊዜ ቀጠሮ ጠይቋል።

የተጠርጣሪ አብዲሳ መገርሳ ጠበቃ በበኩላቸው የተጠረጠረበት ጉዳይ ስለፍንዳታው ለግብረ አበሮቹ ሪፖርት አድርገሃል ተብሎ ነው።

ረጅም ጊዜ ምርመራው የሚወስድ አይደለም ጉዳዩም ዋስትና የሚያስከለከል ባለመሆኑ በዋስ ሊወጣ ይገባል ሲሉ የፖሊስን ተጨማሪ ጊዜ ተቃውመዋል።

ተጠርጣሪ በየነ ቡላ በበኩሉ እኔ በፍቼ ነው የተያዝኩት ሆን ተብሎ እኔን ለማጥቃት የሚደረግ ድርጊት ነው በማለት ከዘርና ከፖለቲካ ጋር አያይዘው ላቀረቡት አስተያየት ፍርድ ቤቱ በችሎት ህጋዊ ድርጅትን መዝለፍ አይፈቀድም ሲል ንግግራቸውን አስቁማል።

ፍርድ ቤቱም ተጠርጣሪዎች ላይ የተገኘ ተጨባጭ ማስረጃ እንዳለ መርማሪ ፖሊስ እንዲያበራራ ጠይቋል።

መርማሪ ፖሊስም ከፍተኛ አመራሮች የሚገኙበት የድጋፍ ሰልፍ በመሆኑ በዋናነትም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድን ለመግደል እና ሌሎች ከፍተኛ ባለሰልጣኖች ላይ ጥቃት ለመሰንዘር የታቀደና የተሞከረበት ይህ ድርጊትን በ160 ንጹሃን ዜጎች ላይ የአካል ጉዳትና የሁለት ሰው ሞት እና ቤተሰቦቻቸውን ማሰብ ያሰፈልጋል ብሏል።

ይህ የወንጀል ድርጊት ከላይኛው አመራር እስከ ታቸኛው አመራር ድረስ ተሳትፎ ያለበት መሆኑን ፖሊስ ጠቅሷል።

በየነ ቡላን በተመለከተ ከሌሎች ከተጠረጠሩ ግብረ አበሮች ጋር በመሆን ቦምቡን እንዴት እንደሚያፈነዱ በመነጋገር በማመቻቸት ቦምቡ እንዲፈነዳ ማስደረጉን የሚጠቁም ማስረጃ እንዳለው ገልጿል።

ሁለተኛ ተጠርጣሪ አብዲሳ መገርሳም ከቦምብ ፍንዳታው በኋላ ፍንዳታው ጉዳት ማን ላይ እንደደረሰና የቦምቡን ጉዳት ሁኔታ ለግብረ አበሮቹ ሪፖርት ማደረጉን የሚያመላከት ማስረጃ አለኝ ሲል ዋስትናቸውንም ተቃውሟል።

የሁለቱንም ጉዳይ የተከታተለው ፍርድ ቤቱ ምርመራው ውስብስብና የወንጀል ድርጊቱ ከባድ ጊዜ የሚጠየቅ መሆኑን በመጥቀስ ለመርማሪ ፖሊስ ምርመራውን አጠናቆ ለመጨረሻ እንዲቀርብ ፖሊስ የጠየቀውን የ14 ቀን ተጨማሪ ጊዜን ፈቅዷል።

በሁለተኛ ደረጃ ችሎቱ የተመለከተው የእነ አብዲሳ ቀነኔ፣ ደሳለኝ ተስፋዬ፣ ጌቱ ግርማና ባህሩ ቶላን ጉዳይ ሲሆን፥ መርማሪ ፖሊስ ከእነዚህ ተጠርጣሪዎች ጋር አብራ ምርመራ ሲከናወንባት የነበረችው ህይወት ገዳ ጉዳይን ማቋረጡን አስታውቋል።

በተመሳሳይ የምራመራ ስራውን ማከናወኑን በመግለጽ ከኤፍ ቢ አይ የቴክኒክ ምርመራን እና መስል ማስረጃን ለማቀረብ የ14 ቀን ጊዜ እንዲሰጠው ጠይቋል።

የአብዲሳ ቀነኔ ጠበቃ በበኩላቸው አብዲሳ የተያዘው ሰው ለመጠየቅ አቤት ሆስፒታል በሄደበት ጊዜ እንጂ ድርጊቱን አልፈፀመም ፖሊስ የድርጊቱ መፈጸምን የሚያሰረዳ ማስረጃ መዝገቡን አቅርቦ ሊያሳይ ይገባል ፖሊስ ምስክር እንዲሆነን የሚያቀርበው ጥያቄ ተገቢ አይደለም ሲሉ በዋስ ሊወጣ ይገባል ሲሉ የፖሊስ ተጨማሪ ጊዜ ጥያቄን ተቃውመዋል።

በተመሳሳይ ሌሎች ተጠርጣሪዎችም የተጨማሪ ጊዜን በመቃወም ከድርጊቱ ጋር ግንኙነት የለንም በማለት ዋስትና እንዲፈቀድላቸው ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል።

ፍርድ ቤቱም የተጠርጣሪዎቹን የተጠረጠሩበት ድርጊት በማስረጃ መረጋገጡን ፖሊስ እንዲያሰረዳ በጠየቀው መሰረት ፖሊስ ጌቱ ግርማ መኖሪያ ቤት ውስጥ በሰኔ 16 የመስቀል አደባባዩ የቦምብ ጥቃት ለማድረስ የተወረወረ አይነት ተመሳሳይ ቦምብ መገኘቱን ገልጿል።

አብዲሳ ቀነኔ ባለው የህክምና ሙያ ተጠቅሞ ቦምቡን አፈንድቶ በራሱ ላይም ጉዳት የደረሰበትን ለማስመለጥ አቤት ሆስፒታል ሄዶ በጀርባ በኩል ለማስመለጥ ነርሶችን ሲያግባባ እንደነበርና ለዚሀም ማስረጃ እንዳለው ፖሊስ ገልጿል።

ተጠርጣሮዎቹ ምንቡን ለማፈንዳት እንዴት፣ የትና በምን ሁኔታ የሚለውን ጉዳይ አስቀድመው መረጃ የተለዋወጡበትን ሆነ ከፈነዳ በኋላ የተለዋወጡበት መረጃም ሆነ ሌሎች ማስረጃዎች አሉኝ ሲል አብራርቷል።

ጉዳዩን የተከታተለው ፍርድ ቤትም ምርመራው ውስብስብና የወንጀል ድርጊቱ ከባድ ጊዜ የሚጠየቅ መሆኑን በመጥቀስ ለመርማሪ ፖሊስ ምርመራውን አጠናቆ ለመጨረሻ ጊዜ እንዲቀርብ ፖሊስ የጠየቀውን የ14 ቀን ተጨማሪ ጊዜን ፈቅዷል።

የምርመራ መዝገቡን ከሁለት ቀን በፊት አቀርቦ እንዲያሳይ አዟል።

Related Articles

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Back to top button