loading
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ኢትዮጵያና ኬንያ የሞያሌ አካባቢን የምስራቅ አፍሪካ የኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ በጋራ እንዲሰሩ ጥሪ አቀረቡ

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ኢትዮጵያና ኬንያ የሞያሌ አካባቢን የምስራቅ አፍሪካ የኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ በጋራ እንዲሰሩ ጥሪ አቀረቡ።

የኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በበኩላቸው አገሮቹ ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር ለመፍጠር ያላቸውን ምቹ ሁኔታ አሟጦ መጠቀም እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡

መሪዎቹ ይህንን ያሉት የኢትዮጵያ የኬንያ ኢኮኖሚ ትስስርን ለማጠናከር በአዲስ አበባ እየተካሄደ ባለው ፎረም ላይ ነው፡፡

ፎረሙ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ሲሆን ከሁለቱ አገሮች ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች በተጨማሪ 100 የሚሆኑ የኬንያ ባለሀብቶች እየተሳተፉበት ይገኛሉ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አቢይ በዚሁ ወቅት ”ኢትዮጵያና ኬንያ በጋራ ከሰሩ የሚሳናቸው እንደሌለ የማራቶን አትሌቶቻችን ምስክሮች ናቸው” ነው ያሉት፡፡

አገሮቹ ያላቸውን የቆየ ግንኙነት ወደጋራ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት መቀየር እንዳለባቸውም ተናግረዋል፡፡

ሁለቱ አገሮች በመሠረተ ልማት በመተሳሰር የሞያሌ አካባቢ የምስራቅ አፍሪካ የኢኮኖሚ ማዕከል ማድረግ እንዳለባቸውም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ለዚህም የኢትዮጵያ መንግስት የሚጠበቅበትን ሁሉ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በበኩላቸው ሁለቱ ሃገራት በጋራ ለመልማት ካላቸው እድል አንፃር የሄዱት ርቀት የሚጠበቀውን ያህል አይደለም። በመሆኑም ያሉትን ምቹ ሁኔታዎች አሟጠን በመጠቀም የዜጎቻችንን ኑሮ ማሻሻል አለብን ብለዋል፡፡ ሁለቱ አገሮች የሚዋሰኑባትን ሞያሌ “የጋራ ከተማና የኢኮኖሚ እንብርት” ለማድረግ የሚያስችል ፕሮጀክት ለመንደፍ መስማማታቸውም ይታወሳል።

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *