loading
አግቦንላሆር እግር ኳስ መጫወት በቃኝ ብሏል

የቀድሞው የአስቶን ቪላ እና እንግሊዛዊ አጥቂ ጋብሪዬል ኢሙትኒንያን አግቦንላሆር በ32 ዕድሜው እግር ኳስ ከመጫወት መገለሉን አስታውቋል፡፡

አግቦንላሆር በቻምፒዮንሽፑ እየተካፈለ ከሚገኘው አስቶን ቪላ ጋር ባለፈው የውድድር ዓመት ማብቂያ ከተለያዬ በኋላ፤ ክለብ አልባ የነበረ ሲሆን ከታህሳስ ወር 2017 በኋላ ጨዋታ አላደረገም፡፡

ተጫዋቹ በ17 ዓመት የቪላ ቆይታው፤ ተሰልፎ በተጫወተባቸው 391 ጨዋታዎች 86 ጎሎችን አስቆጥሯል፤ በአጠቃላይ የእግር ኳስ ህይወቱ ደግሞ በ401 ጨዋታዎች ላይ ተሰልፎ መጫወት ችሏል፡፡

ከዋናው የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድንም ጋር ቆይታ የነበረው ቢሆንም በሶሰት ጨዋታዎች ብቻ ተሰልፎ አንድም ግብ ማስቆጠር አልቻም፡፡ በአንፃሩ ለእንግሊዝ ከ21 ዓመት ብሔራዊ ቡድን በ16 ግጥሚያዎች 4 ጎሎችን አበርክቷል፡፡

ውልደቱን በርሚንግሃም ያደረገው እንግሊዛዊው አጥቂ፤ የአስቶን ቪላ አካዳሚ ውጤት ቢሆንም ለዋናው ቪላ ቡድን ከመጫወቱ በፊት በእንግሊዝ የታችኛው የሊግ ውድድር ዋትፎርድ እና ሼፊልድ ዌነስደይ በውሰት ውል አሳልፏል፡፡

አግቦንላሆር ‹‹ ከእግር ኳስ በይፋ መገለሌን የማስታውቅበት ጊዜ ላይ እገኛለሁ፤ ከዚህ በኋላ አስቶን ቪላን እንደ ደጋፊ ሁኔ እመለከታለሁ›› ሲል በኢንስታግራም ገፁ አስታውቋል፡፡

‹‹ለሁሉም የክለቡ ደጋፊዎች፣ በታላቁ ክለብ አብረውኝ ለሰሩ ሰራተኞች እና የቀድሞ የቡድን ጓደኞቼን ላመሰግን እወዳለሁ›› ሲል ጨምሮ ተናግሯል፡፡

 ከዚህ በኋላ ለሌላ ክለብ አሊያ ከአስቶን ቪላ ተቃራኒ ሁኖ መጫወት የማይታሰብ ነገር ነው፡፡ ወደፊት የሚሆነውን አብረን እናያለን ሲል ጋብሪዬል አግቦንላሆር ገልጧል፡፡

እንደ ቢቢሲ ዘገባ የአስቶን ቪላ ክለብ ከ2007-08 እስከ 2009- 10 ባሉት ሶስት ተከታታይ የውድድር ዓመት፤ በፕሪምየር ሊጉ ስድስተኛ ደረጃን ይዞ ሲያጠናቅቅ የእንግሊዛዊው ተጫዋች ሚና ጉልህ ነበር፡፡  

በተጨማሪም ከክለቡ ጋር በ2010 የሊግ ካፕ ፍፃሜ ደርሶ በማንችስተር ዩናይትድ ሲሸነፍ፤ ተቀያሪ ሁኖ ወደ ሜዳ በገባበት የ2015 የኤፍ ኤ ዋንጫ ፍፃሜ በአርሰናል ተረትቶ ዋንጫውን የተነጠቀበት ጨዋታ ትልቁ የተጫዋቹ ስኬቱ ነበር፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *