loading
የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ተስተካካይ ጨዋታዎች የሚካሄዱበት ቀን ታውቋል

በሊጉ የ21ኛ ሳምንት መርሀግብር በደጋፊ ጥል ምክንያት ያልተካሄዱ ሁለት ጨዋታዎች በመጪው ሀሙስ እንደሚደረጉ እና በዕለቱ ሊካሄዱ ቀጠሮ ተይዞላቸው የነበሩት የ22ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ደግሞ ወደ ማክሰኞ ተሸጋግረዋል ሲል የኢትዮጵያ አግር ኳስ ፌዴሬሽን የሊግ ኮሚቴ አስታውቋል፡፡

በዕለተ ቅዳሜ በደቡብ ፖሊስ እና ወላይታ ድቻ መካከል ሀዋሳ ከተማ ላይ ሊካሄድ የነበረውና ከጨዋታው በፊት በተከሰተ የደጋፊዎች ግጭት ችግር ሳይከናወን የቀረ ሲሆን ግጥሚያው በአዲስ አበባ ስታዲየም ላይ በ11:00 በዝግ ስታዲየም ይደረጋል ተብሏል።

ዕሁድ ዕለት ደግሞ በሀዋሳ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ መካከል በሀዋሳ ሰው ሰራሽ ስታዲየም ላይ ሊደረግ የነበረው ፍልሚያ ከተማዋ ላይ በነበረው የፀጥታ ስጋት ምክንያት ሳይካሄድ የቀረ ሲሆን በዕለተ ሀሙስ አሰላ ላይ በ9:00 ሰዓት እንዲካሄድ ተወስኗል።

ሀሙስ ሊካሄዱ የነበሩት የ22ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ማሻሻያ ተደርጎባቸው ወደ ቀጣዩ ሳምንት ማክሰኞ ተገፍተዋል፡፡

ሁሉም የሳምንቱ መርሀግብር ግጥሚያዎች ማክሰኞ ሲካሄዱ ክልል ስታዲየሞች ላይ በተመሳሳይ 9፡00 ጅማ አባ ጅፋር ጅማ ከተማ ላይ ከ ሲዳማ ቡና ፤ ሽረ ላይ ስሑል ሽረ ከ ሀዋሳ ከተማ፤ አዳማ ከተማ በአዳማ አበበ ቢቂላ ስታዲየም ከ ኢትዮጵያ ቡና፤ ባህር ዳር ከተማ በባህር ዳር ግዙፍ ስታዲየም ላይ ከ ደቡብ ፖሊስ ሲጫወቱ፤ ወላይታ ድቻ ሶዶ ላይ ከ መከላከያ፤ ትግራይ ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከ ደደቢት ሲጫወቱ ጎንደር ላይ ፋሲል ከነማ ድሬዳዋ ከነማን ያስተናግዳሉ፡፡

በአዲስ አበባ ስታዲየም ደግሞ በሳምንቱ ተጠባቂ ፍልሚያ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ መቐለ 70 እንደርታ 11:00 ሰዓት ሲል ይገናኛሉ፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *